አዲሱ የመንግስት የኤሌክትሮኒክስ ግዥ ስርዓት ብልሹ አሰራርን የሚያስወግድ ነው ተባለ

የመንግሥት ግዥና ንብረት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ሀጂ ኢብሳ ለአዲስ ቻምበር የማኔጅመንት አባላት ባደረጉት ገለፃ አዲሱ የመንግስት የኤሌክትሮኒክስ ግዢ በዘርፉ የሚስተዋለውን ብልሹ አሰራርን የሚያስወግድ ነው ብለዋል ፡፡
በኤሌክትሮኒክስ የሚካሄደው ጨረታና ግዢ ወጪን ይቀንሳል፣ ቅልጥፍናን እና ግልጽነትንም እንደሚያሰፍን ተናግረዋል፡፡ ለአብነትም አለም አቀፍ ተሞክሮ እንደሚያሳየው የመንግስት የኤሌክትሮኒክ ግዥ የተጠቀሙ ሀገራት ከ5-25% ከበጀታቸው መቆጠብ ችለዋል፡፡
አንዳንድ ጥናቶች እንደሚያመላክቱት ከ60-70% የሚሆነው የሀገራችን የመንግስት በጀት ለግዥ ይውላል ፡፡
የአዲስ ቻምበር ም/ዋና ፀሐፊ አቶ ዘካርያስ አሰፋ በበኩላቸው አዲስ ቻምበር በኤሌክትሮኒክስ የሚካሄደውን የግዢ ግብይት ለአባላቱ ለማስተዋወቅ ዝግጁ መሆኑን ገልፀዋል፡፡
በተለይም በአቅም ግንባታ ስልጠና ዙርያ በጋራ እንደሚሰሩ ተመላክቷል፡፡ በዚህ አመት 72 የመንግስት መስርያ ቤቶች የኤሌክትሮኒክስ ግዢ ሂደት እንደሚጀምሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡
በተያያዘ ዜና የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን ለመንግስት ግዥ አቅራቢዎች አዲስ በዘረጋው/ የአቅራቢነት ምዝገባ አገልግሎት/ አሠራር ዙሪያ ግንዛቤ ለመፍጠር ጥቅምት 15 ቀን 2015 ዓ.ም ከጠዋቱ 2፡30 ጀምሮ ላምበረት በሚገኘው ሀይሌ ግራንድ ሪዞርት የግንዛቤ ማስጨበጫ ፕሮግራም አዘጋጅቷል፡፡
የሚመለከታችሁ የግሉ ዘርፍ አቅራቢዎች ሀላፊዎች/ባለቤቶች/ ባለሙያዎች ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡