ፎረሙ ኢትዮጵያ ያላትን ሰፊ የኢንቨስትመንት አማራጮች እንድንመለከት አስችሎናል-የቤልጂየምና ሉግዘምበርግ ንግድ ምክር ቤት ዋና ስራ አስፈፃሚ

አዲስ አበባ፤ግንቦት 27/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮ-ቤልጅየም የቢዝነስ ፎረም ኢትዮጵያ ያላትን ሰፊ የኢንቨስትመንት አማራጮች እንድንመለከት አስችሎናል ሲሉ የቤልጂየምና ሉግዘምበርግ ንግድ ምክር ቤት ዋና ስራ አስፈፃሚ ቶማስ ዴቡል ገለጹ፡፡

የኢትዮ-ቤልጅየም የቢዝነስ ፎረም ግንቦት 25 ቀን 2017 ዓ.ም ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎች እና አምባሳደሮች በተገኙበት በአዲስ አበባ ከተማ መካሔዱ ይታወቃል።

በፎረሙ ኢትዮጵያውያንና ከቤልጂየም የመጡ በተለያዩ የኢንቨሰትመንት ዘርፎች የተሰማሩ ነጋዴዎች ምርቶቻቸውንና አገልግሎታቸውን አስተዋውቀዋል፡፡

በማጠቃለያው፥ የአዲስ አበባ ንግድና የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት እና የቤልጄዬም ንግድ ምክር ቤት በተለያዩ መስኮች በጋራ መስራት በሚችሉባቸው ጉዳዮች ላይ የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል፡፡

የቤልጄምና የሉግዘምበርግ ንግድ ምክር ቤት ዋና ስራ አስፈጻሚ ቶማስ ዴቡል በዚሁ ወቅት፤ ፎረሙ ኢትዮጵያ በፈጣን ኢኮኖሚያዊ እድገት ላይ መሆኗንና ያላትን ሰፊ የኢንቨስትመንት አማራጮች እንድንመለከት አስችሎናል ብለዋል፡፡

ከኢትዮጵያውያን ነጋዴዎች ጋርም ይበልጥ እንድንተዋወቅ እና የልምድ ልውውጥ ለማድረግ ትልቅ እድል እንደፈጠረላቸውም አመላክተዋል፡፡

ስምምነቱ በሀገራቱ መካከል ያለውን የንግድና ኢንቨስትመንት እድሎች ለማሳደግ እና ለማስተዋወቅ የሚያስችል መሆኑንም ገልጸዋል፡፡

በግብርና፣በታዳሽ ሃይል፣በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ፣ በጤና፣ በሌሎች ዘርፎች ላይ ለመሰማራት ፍላጎት እንዳላቸው አመላክተዋል፡፡

የአዲስ አበባ ንግድና የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ዘሐራ መሐመድ በበኩላቸው፥አዲስ ቻምበር በአገራቱ ነጋዴዎች መካከል እንደ ድልዲይ ሆኖ የማገናኘት ሚናዎችን ይወጣል ብለዋለ፡፡

ስምምነቱ ኢትዮጵያ ከቤልጅዬም እና ከሉግዘምበርግ ጋር ያላትን የቢዝነስ ትስስር ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር መሆኑን ተናግረዋል፡፡

በቀጣይ የቤልጅየም ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ያለውን የኢንቨስትመንት እድል እንደሚጠቀሙ እና የንግድ ለንግድ ግንኙነት እንዲጠናከር ምክር ቤቱ ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥር ተናግረዋል፡፡
#Ethiopian_News_Agency
#ኢዜአ
#Ethiopia

wpChatIcon
wpChatIcon