post

የአዲስ ቻምበር የ 75ኛ አመት የምስረታ ክብረ በአል መዝጊያ መርሀግብር ለተለያዩ አካላት እውቅና በመስጠት ተጠናቀቀ ፡፡

በ1939ዓም በቻርተር የተቋቋመው የአዲስ አበባ ንግድ ም/ቤት ዛሬ ላይ የ75 አመት አንጋፋ ተቋም ሆኗል፡፡ ታዲያ ምክር ቤቱ በስኬትና በውጣ ውረድ የታጀበው የ75 አመታት የምስረታ በአሉ ለተለያዩ አጋር አካላት፣ የቻምበር ፕሬዚዳንቶች፣ም/ፕሬዚዳንቶች፣ የቦርድ አባላት እና ሰራተኞች እውቅና በመስጠት ተጠናቀቀ፡፡ ሰኔ 23 ፣2014 በስካይ ላይት ሆቴል በተካሄደው የማጠቃለያ ስነስርአት ከምስረታው አንስቶ የንግድ ምክር ቤቱ በየዘመናቱ ካጋጠመው ፈተናዎችና መሰናክሎች አልፎ አሁን ያለበት ደረጃ ላይ እንዲደርስ አስተዋጽኦ ላበረከቱ ግለሰቦችና ባለድርሻ አካላት የዋንጫ፣የሜዳልያና ሰርቲፊኬት እውቅና ተሰጥቷል፡፡ ይህ የ75ኛ አመት የምሥረታ በዓሉ ባማረና በደመቀ ሥነስርዓት እንዲከበር በአብይ ኮሚቴ አና ሌሎች 16 ንዑሳን ኮሚቴዎች ተቋቁመው ልዩ ልዩ ተግባራትን ሲያከናውኑ ቆይተዋል፡፡ ከእነዚህ መካከል የም/ቤቱን ወጥ ታሪክ የሚያወሳ አዲስ መጽሐፍ ማዘጋጀት ሲሆን መጽሐፉ በገለልተኛ እና ልምድ ባላቸው ባለሙያዎች የተጻፈ ሲሆን ንግድ ም/ቤቱ በእነዚህ ረጅም አመታት ውስጥ በትውልድ የቅብብሎሽ ሰንሰለት ላይ ያለፈባቸውን መልካም እና ፈታኝ ሁኔታዎችን የሚዘክርና ፣የወደፊቱን የጉዞ አቅጣጫ የሚጠቁም ሰነድ እንዲሆን ተደርጓል፡፡

ሌላውና አበይት ስራ በ1993 ዓም የተዘጋጀው እና ዘወትር የአዲስ ቻምበር የሬድዮ ፕሮግራም መክፈቻ ሆኖ ሲያገለግል የቆየው እና በሕዝብ ጆሮ የተለመደው ‘ ራዕያችን’ የተሰኘው ዝማሬ መሠረቱን ሳይለቅ በተሻለ የድምጽ ጥራት እና ባማረ ሙዚቃዊ ቅንብር እንደገና ዘምኖ፣ተሻሽሎና ተዘጋጅቶ እንዲወጣ ተደርጓል ተብሏል፡፡
በተለያዩ የመንግስት ስርአቶች ውስጥ የንግዱ ህብረተሰብ እና ምክር ቤቱ ያሳለፏቸውን ውጣ ውረዶች፣ እድሎቹና ተስፋዎቹን የሚያሳይ ‘የነጋዴው ዋርካ’ በሚል ዶክመንታሪ ፊልም በፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ተዘጋጅቶ ለተመልካች በቅቷል፡፡

በአሉ በተለያዩ የንግድና ኢንቨስትመንት ዙሪያ የሚያጠነጥኑ ታላላቅ የፖሊሲ ፓናሎችና ሲምፖዚየሞች የተካሄዱበትም ነበር፡፡ በስካይ ላይት ሆቴልና በሂልተን ሆቴል ለ3 ቀናት ከተካሄዱት ፓናሎቹና ሲምፖዚየሞቹ መካከል በኢትየጵያ የግሉ ዘርፍ ልማትና ከባቢ የፖሊሲ ሁኔታዎች፣ ህገወጥ ንግድና የተወዳዳሪነት ፈተናዎች፣ የህጎችና ደንቦች አወጣጥ በግሉ ዘርፍ ልማት ፣ በሴቶች የሚመራ የቢዝነስ አመራር፣ የሶሻል ኢንተርፕራይዝ እድሎችና ፈተናዎች እንዲሁም ዛሬ የተካሄደው የንግድ ማህበራትና ተቋማት በኢትየጰያ ኢኮኖሚ ውስጥ ያላቸው ሚና የመሳሰሉት ርእሶች ይገኙበታል፡፡ በእነዚህንም ፓናሎች ታዋቂ ምሁራን፣የፖሊሲ አውጪዎች እና የግሉ ዘርፍ ተዋንያን ሀሳባቸውን አቅርበዋል፡፡
በአጠቃላይ ይህ ክብረ በአል ምክር ቤቱ በመጪው ዘመን የሰነቀውን ተስፋ የሚያመላክትበትና የንግዱ ማህበረሰብ እንደራሴነቱን ከወትሮው በተለየ ሁኔታ የሚያሳይበት እና ካልኪዳኑን የሚያድስበት መሆኑን ንግድ ምክር ቤቱ ገልጿል፡፡ በተለይ በአሉ እንዲህ በሰመረ ሁኔታ እንዲከበር አስተዋጽኦ ላበረከቱ አጋር ተቋማት ልባዊ ምስጋናውን አቅርቧል፡፡

post

የአዲስ አበባ ንግድና የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት የተመሰረተበትን 75ኛ ዓመት እያከበረ ነው።

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 21፣ 2014 የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ለሃገሪቱ የንግድ ስርዓት ማደግና መሳለጥ የራሱን አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡ የአዲስ አበባ ንግድና የዘርፍ ማኀበራት ምክር ቤት/ አዲስ ቼምበር/ የ75ኛ ዓመት ክብረ በዓሉን በስካይ ላይት ሆቴል እያካሄደ ነው፡፡
በ1939 ዓ.ም የተመሰረተዉ አዲስ ቻምበር ባለፉት 75 ዓመታት ዘርፈ ብዙ ተግባራትን ማከናዉን የገለጹት የምክር ቤቱ ጸኃፊ አቶ ሺበሺ ቤተማርያም ምክር ቤቱ ለንግዱ ማህበረሰብ እዉነተኛ ድምጽ መሆኑን በተግባር አረጋግጧል ነዉ ያሉት:: ምክር ቤቱ በተጽእኖዎች ሳይበገር ዘመን ተሸጋሪ ተቋም መሆኑን አሳይቷል ብለዋል ዋና ጸኃፊዉ፡፡
የንድ ምክር ቤቱ ፕሬዚዳንት ወይዘሮ መሰንበት ሸንቁጤ በበኩላቸዉ የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት 75ተኛ አመት ምስረታዉን ሲያከብር ለመጪው ዘመን የሰነቀውን ተስፋ የሚያመላክትበትና የንግዱ ማህበረሰብ እንደራሴነት ቃልኪዳኑን የሚያድስበት እንደሚሆን ገልጸዋል፡፡
የሃገሪቱን የንግድ የኢንቨስትመንት የኢኮኖሚ ሁኔታዎች እየተከታተሉ የፖሊሲና ሌሎች ምክረሃሳቦችን ለመንግስ በማቅረብ ቻምበር ሃላፊነቱን በተግባር እየገለጸ መምታቱም በመድረኩ ተወስቷል፡፡ የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሃሰን መሃመድ እንዳሉትም አዲስ ቻምበር ከተመሰረተ ጊዜ ጀምሮ በሀገሪቱ የንግድ እንቅስቃሴዎች ላይ ከፍተኛ ሚና ያለዉን የንግድ ማህበረሰብ በመወከል ጥቅሞቹና መብቶቹ እንዲከበሩ ያላሰለሰ ጥረት አድርጓል ብለዋል፡፡ የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ለሃገሪቱ የንግድ ስርዓት ማደግና መሳለጥ የራሱን አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑንም ሚኒስትር ዴኤታዉ የገለጹት፡፡ የአዲስ ቻምበርን የ75 ዓመት ጉዞ የሚያሳይ የፎቶግራፍ ኤግዚቢሽንም ተከፍቷል፡፡
post

ሀገር አቀፍ የምክክር ኮሚሽን ከንግዱ ማህበረሰብ ተወካዮች ጋር ውይይት አካሄደ

ሀገር አቀፍ የምክክር ኮሚሽን በአዲስ አበባ ንግድ እና ዘርፍ ማህበራት ም/ቤት አመቻችነት ከንግዱ ማህበረሰብ ተወካዮች ጋር መክሯል ። ኮሚሽኑ ሁሉን አቀፍ የምክክር መድረክ ለማድረግ ዝግጅት ላይ ሲሆን የንግዱ ማህበረሰብንም ያካትታል ተብሏል ። በቅርቡ በሀገሪቱ ሰላምና እርቅን ለማስፈን ይደረጋል በተባለው የምክክር መድረክ ላይ ከንግዱ ማህበረሰብ መሪ ሀሳቦችን ማቅረብ እና ንቁ ተሳትፎ ይጠበቃል ተብሏል። የአዲስ አበባ ንግድ እና ዘርፍ ማህበራት ም/ቤት ፕሬዚዳንት ወ/ሮ መሠንበት ሸንቁጤ ንግድን ለማሳለጥ ሰላም ወሳኝነት አለው ያሉ ሲሆን ም/ቤቱ በምክክር ሒደቱ ውስጥ የሚጠበቅበትን ድርሻ እንደሚወጣ አረጋግጠዋል ።
በውይይቱ ላይ የምክክር ኮሚሽኑ ኮሚሽነር አምባሳደር መሀመድ ድሪር ፤ ኮሚሽነር ዶ/ር ዮናስ አዳዬ ፤ የአዲስ አበባ ንግድ እና ዘርፍ ማህበራት ም/ቤት ፕሬዚዳንት ወ/ሮ መሠንበት ሸንቁጤ እና ዋና ጸሀፊው አቶ ሺበሺ ቤተማርያም እንዲሁም  የንግዱ ማህበረሰብ አባላት ተገኝተዋል ። የም/ቤቱ ዋና ጸሀፊ አቶ ሺበሺ ቤተማርያም በበኩላቸው የኮሚሽኑን አላማ የሚደግፍ ” ሰላም ለቢዝነስ ቢዝነስ ለሰላም ” በሚል ርእስ በቅርቡ የውይይት መድረክ የማድረግ እቅድ እንዳለው ጠቁመዋል ።
post

የአዲስ ቻምበርን የ75 ዓመት ጉዞ የሚያሳይ የፎቶግራፍ ኤግዚቢሽን ተከፈተ

የአዲስ አበባ ንግድና የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት (አዲስ ቻምበር) የተመሰረተበትን 75ኛ ዓመት እያከበረ ነው። በወቅቱ የአዲስ ቻምበር 75 ዓመት ጉዞ የሚያሳይ የፎቶግራፍ ኤግዚቢሽን በስካይላይት ሆቴል ተመርቆ ተከፍቷል። ኤግዚቢሽኑን የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሀሰን መሐመድና የአዲስ ቻምበር ፕሬዚዳንት ወይዘሮ መሰንበት ሸንቁጤ ከፍተውታል። የፎቶ ኤግዚቢሽኑ ላይ 156 ፎቶዎች ለዕይታ ቀርበዋል። የአዲስ አበባ ንግድና የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት የፋሺስት ወረራ ካበቃ በኋላ በ1939 ዓ.ም የንግዱን ዘርፍ ተወዳዳሪነት ለማሳደግ የተቋቋመ ምክር ቤት ነው።