የአዳማ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት አመራሮች ከአዲስ ቻምበር ጋር በጋራ መስራት በሚችሉበት ዙሪያ ተወያዩ ::

12 የቦርድና የፅ/ ቤት ሰራተኞችን የያዘው የአዳማ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት በአዲስ ቻምበር ተገኝቶ የሁለቱ ንግድ ምክር ቤቶች በቀጣይ በጋራ አብረው መስራት በሚችሉበት ሀኔታ ላይ መክረዋል ፡፡

የአዲስ ቻምበር ዋና ፀሀፊ አቶ ሺበሺ ቤተማርያም ምክር ቤታቸው የንግድ ማህበረሰብ አገልግሎት በመሰጠት 75 ዓመታትን ማስቆጠር ያቻለ አንጋፋ ተቋም መሆኑን ገልፀዋል ፡፡

ከአነስተኛ ቢዝነስ እስከ ኮርፖሬትየኢኮኖሚ ዘርፎች የተሰማሩ 17ሺ አባላት እንዳሉት የጠቀሱት አቶ ሺበሺ ፤ ለአባላቱ የተለያዩ የቢዝነስ ድጋፍ ከመስጠት ባለፈ የግሉን ዘርፍ ከመንግስት ጋር በማገናኝት እንደ ድልድይ ሆኖ እየሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል ፡፡

አክለውም አዲስ ቻምበር የግሉን ዘርፍ አንገብጋቢ ጉዳዮችን በማንሳት እልባት እንዲያገኙ ባለድርሻ ከሆኑ ብሄራዊ ባንክ ፣ ገንዘብ ሚንስቴር ፣ ንግድና እና ኢንዱስትሪ ሚንስቴር ጋር እየሰራ መሆኑንም ገልፀዋል ፡፡

አሁን ላይ የአሰራር ለውጥ በማድረግ ዘመኑን የሚፈልገውን አገለግሎት ለመሰጠት የሚያስችለው የሰው ኃይል አደረጃጀት ተግባራዊ ማድረጉንም በልምድ ልውውጥ መድረኩ አንስተዋል ፡፡

የአዲስ ቻምበር አስራር ምን ይመስላል የሚለውን በተመለከተ የምክር ቤቱ የተለያዩ ክፍሎች የመመሪያ ስራ አስኪያጆች አማካኝነት ገለፃ ተደርጎላቸዋል ፡፡

የአዳማ ንግድ ምክር ቤት የቦርድ አባላት እና የፅ/ቤት ኃላፊዎች በበኩላቸው በአዲስ ቻምበር ተገኝተው ያደረጉት ውይይት መልካም ተሞክሮ ያገኙበት መሆኑን ጠቅሰው ለቀጣይ ስራቸው እንደ ግብዓት እንደሚጠቀሙበት ገልፀዋል ፡፡

በተለይም ምክር ቤቱ ሴት ሰራተኞች ወደ አመራር ለማምጣት የሰጠው ትኩረት የሚበረታታና የሚደገፍ መሆኑን ጠቅሰው ይህንን ለሌሎች ቻምበሮችም እንደ ተሞክሮ ሊወሰድ ይገበል ብለዋል ፡፡

በአጠቃላይ ከተደረገላቸው ገለፃና ካዩት የንግድ ምክር ቤቱ አሰራር ሳቢያ በተለይ በስልጠና ፣ በሰው ኃይል ፣ በፕሮጀክት ፣ ንግድ ትርዒት ላይ ትልቅ ተሞክሮ አግኝተንበታል ብለዋል ፡፡

አዲስ ቻምበር በንግድ ትርዒት ዘርፍ ላይ ያለውን ረጀም ዘመን ያሰቆጠረ ተሞክሮ ለአዳማ ንግድ ምክር ቤት ለማካፍልና አብሮ ለመሰራት ያሳየው ፍላጎት አድንቀዋል ፡፡

አዳማ ንግድ ምክር ቤት በቀጣይ ነሀሴ ወር የተመሰረተበትን አምሳኛ አመት ሲያከብር አዲስ ቻምበር ከራሱ ተሞክሮ በመነሳት የቴክኒክና የሃሳብ ድጋፎችን እንደሚያደርግ አቶ ሺበሺ አረጋግጠዋል ፡፡

የአዲስ ቻምበር እራሱን በለውጥ መንገድ መምራት ከጀመረ ወዲህ ከደብረ ብርሃንና ፣ አሰላ ንግድ ምክር ቤቶች ቀጥሎ የአዳማ ንግድ ምክር ቤት የልምድ ልውውጥ ያደረገ ሶስተኛው የከተማ ንግድ ምክር ቤት ነው ፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *