የስራ እድል በመፍጠርና የውጭ ምንዛሬን ማዳን ላይ ከፍተኛ አስተዋፆ ያለውን የአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍን ለመደገፍ ቁርጠኛ መሆኑን የአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ አስታወቀ ፡፡

የአዲስ አበባ የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት 16ተኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤው ጥር 02 ፣2016 ዓ.ም አካሂዷል ፡፡
የቢሮው ተወካይ አቶ መከታው አዳፍሬ ጉባኤውን ሲያስጀምሩ ባደረጉት ንግግር ፣ የአምራች ኢንዱስትሪው ችግሮችን በመለየት ተወዳዳሪነቱን ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል ፡፡
በተለይም ተወዳዳሪነትን በሚያሳድጉ የጨርቃ ጨርቅ ፣ ቆዳና ፣ ቆዳ ውጤቶች ፣ ምግብና ፣ ኬሚካልና ማዕድን ውጤቶች ለሚያመርቱ መስሪያ ቦታዎችን ከተማ አስተዳደሩ ማመቻቸቱን ተናግረዋል ፡፡
የከተማ አስተዳዳሩ ንግድ ቢሮ ከዘርፍ ምክር ቤቱ ጋር ተቀራርበንና ተቀናጅተን በመስራት ዘርፉን ለማሳደግ በጋራ እንስራ ሲሉ ጥሪ አቅርበዋል ፡፡
የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ፕሬዝዳንት አቶ ፋሲካው ሲሳይ በበኩላቸው የአባላትን መብትና ጥቅምን ለማስከበር ከንግድ ፣ ገቢዎች ፣ እና መሰል ቢሮዎች ጋር የአድቮኬሲ ስራ በመስራት ችግሮች እንዲፈቱ ተስርታል ብለዋል ፡፡
በዚህም ያለአግባብ ታሽገው የነበሩ ጋራዥ ድርጅቶች ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመነጋገር ችግሮቻቸውን በማስረዳት እንዲፈታ መደረጉ አንዱ መሆኑን አቶ ፋሲካ ጠቅሰው ፤
ሌላው በሽክላ ስራ ዘርፍ የተሰማሩ አባላት ላይ አምስት አመት ሞልቷችኋል በሚል ከሼድ ልቀቁ መባሉን ተከትሎ የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በጋራ በመስራት ባሉበት እንዲቆዩ መደረጉን ተናግረዋል ፡፡
አዋጅ ቁጥር 341/ 95 ማሻሻያ በተመለከተ ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤቱ በንግድና ዘርፍ ማህበራት ም/ቤት ማቋቋሚያ ረቂቅ አዋጅ ላይ ውይይት መደረጉን አቶ ፋሲካው ተናግረዋል ፡፡
አባላቱንና ባለድርሻ አካላት ረቂቅ አዋጅን በተመለከተ የተሰጡ አስተያየትና ሃሳባቸውን በማጠናከር ለንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚንስቴር መቅረቡን የ2015 ዓ.ም ሪፖርት ለጉባኤው ገልፀዋል ፡፡
ጉባኤው የዘርፍ ምክርቤቱን የ2015 ዓ.ም በጀት አመት አፈፃፀም ሪፖርት እና የኦዲት ሪፖርቶች ከቀረበለት በኃላ ውይይት ተደርጎበት በሙሉ ድምፅ ፀድቋል ፡፡