አዲስ ቻምበር እና ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት በጋራ ለመስራት የሚያስችላቸውን ሰነድ ተፈራረሙ፡፡

በአዲስ ቻምበር ጽ/ቤት በተከናወነው የፊርማ ስነ ስርአት ላይ ስምምነቱ የምክር ቤቱን አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ እንዲሁም አቅሙን ለመጠቀም እንደሚያግዝ ተጠቁሟል፡፡

የአዲስ ቻምበር ዋና ጸሃፊ አቶ ሺበሺ ቤተማርያም እንዳሉት ምክር ቤቱ ዘርፈ ብዙ አገልግሎቶችን ለንግዱ ማህበረሰብ የሚሰጥ እና ጥናትን መነሻ ያደረጉ የተሟሉ የቢዝነስ መረጃዎች የሚገኙበት በመሆኑ ስምምነቱ የሁለትዮሽ ተጠቃሚነትን ሊያጠናክር እንደሚችል አንስተዋል፡፡

የፋና ብሮድካስት ኮርፖሬት ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ አድማሱ ዳምጠው በበኩላቸው ተቋማቸው በመረጃ የበለጸገ ማህበረሰብን ለመፍጠር የሚሰራ መሆኑን አንስተው ፡መረጃዎቹ እውቀት ላይ የተመሰረቱ መሆን እንዲችሉ ከማድረግ አኳያ አዲስ ቻምበር ባለው እምቅ አቅም ሊያግዛቸው እንደሚችል ተናግረዋል ::

በተጨማሪም አዲስ ቻምበር የሚያከናውናቸውን ተግባራት ብቻ ሳይሆን እንደ ሃገር የሚከናወኑ የንግድ እንቅስቃሴዎች ቀጥተኛ እና በእውቀት ላይ የተመሰረቱ እንዲሆኑ መስራት ላይ ሃላፊነት ያለባቸው መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡

በሁለቱ ተቋማት መካከል የተደረገው ስምምነትም ወደመሬት ወርዶ ተግባር ላይ እንዲውል ኮሚቴ በማዋቀር እና እቅዶችን በማውጣት በመጭው 2016 ዓ.ም ተግባር ላይ እንዲውል ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *