የደብረ ብርሃን ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክርቤት ከአዲስ ቻምበር ጋር የልምድ ልውውጥ አካሄደ

ሰባት አባላት ያሉት የደብረ ብርሃን ንግድ ምክር ቤት የቦርድ አባላት ከአዲስ ቻምበር ፕሬዝዳንት ወ/ሮ መሰንበት ሽንቁጤና የፅህፈት ቤቱ ከፍተኛ የማኔጅመንት አባላት ጋር በጋራ መስራት በሚችሉበት ሁኔታ ላይ መክረዋል ፡፡
የአዲስ ቻምበር ፕሬዝዳንት ወ/ሮ መሰንበት ሸንቁጤ የደብረ ብርሃን ንግድ ምክር ቤት እንዲጠናከር ንግድ ምክር ቤታቸው አስፈላጊውን ሁሉ እገዛ ያደረጋል ብለዋል ፡፡
ምክር ቤታቸው ጠንካራ መሆን የቻለው ጠንካራና ብቃት ያላቸው ሰራተኞች ስላሉት መሆኑን ጠቅሰው ፤የደብር ብርሃን ከተማ ንግድ ምክር ቤትም የአዲስ ቻምበርን ተሞክሮ ቢወሰድ ሰኬታማ እንደሚሆን ጠቁመዋል ፡፡
የምክር ቤቱ ዋና ፀሀፊ አቶ ሺበሺ ቤተ ማርያም በበኩላቸው በፕሮጀክት ቀረፃ ፣ በስልጠና ፣ በንግድ ትርኢት ላይ ከደብር ብርሃን ንግድ ምክር ቤት ጋር በጋራ እንሰራለን ብለዋል ፡፡
የደብረ ብርሃን ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት የቦርድ አመራሮች በበኩላቸው አባላትን በማፈራት ፣ የገቢ ምንጭን በማሳደግና ፕሮጀክትን በመቅረፅ ረገድ የአዲስ ቻምበርን ተሞክሮ ለቀጣይ ስራቸው እንደሚጠቀሙበት አመልክተዋል ፡፡