ንግድ ምክር ቤቱ የባንኩ ዘርፍ ለውጭ ኢንቨስተሮች መከፈቱን አስመልክቶ እየመከረ ነው

ጥቅምት 18/2015 (ዋልታ) የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት የባንኩ ዘርፍ ለውጭ ኢንቨስተሮች መከፈቱን በማስመልከት ምክክር እያካሄደ ይገኛል፡፡
በመድረኩ ላይ የባንኩ ዘርፍ ለውጭ ኢንቨስተሮች መከፈቱ ያለው ጥቅምና ተግዳሮቶች እንዲሁም የውጪና የሀገር ውስጥ ባንኮችን አዋህዶ መሄዱ ላይ ሊተኮርበት በሚገቡ ጉዳዮች ላይ ውይይት እየተካሄደ ነው።
የባንኩን ዘርፍ ለውጭ ኢንቨስተሮች ክፍት ማድረግ ባንኮች ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ዕድል ይፈጥራል የተባለ ሲሆን ብድርና ቴክኖሎጂዎችን በማስፋት የወጪና ገቢ ንግዱ እንዲሳለጥ ያግዛልም ተብሏል፡፡
በተጨማሪም ውድድሩ ዓለም አቀፍ ልምዶችን ለመቅሰም ዕድል የሚፈጥርም ቢሆንም የመንግስትና ብሔራዊ ባንክ ውሳኔ ድንገተኛና ጊዜውን የጠበቀ እንዳልሆነም ተነስቷል፡፡
ባንኮቹ ከመጡ በኋላ ምን አይነት ቁጥጥር መደረግ አለበት በሚለው ጉዳይ ላይ ብሔራዊ ባንክ ፖሊሲና ስትራቴጂ ቀርፆ መንቀሳቀስ አለበት ተብሏል።
የውጪ ባንኮቹ በመምጣታችው ሊከሰቱ የሚችሉ ተግዳሮቶችን በማጤን፣ በመገምገምና በሚያስገኙት ውጤት ላይ አተኩሮ መሰራት አለበት ተብሏል።